ነገሩ ሁሉ እንደ ጥርስ ነው መሰል እህል ያላመጠበትን የመጀመሪያ ቀን የሚያስታውስ የለም።

ነገሩ ሁሉ እንደ ጥርስ ነው መሰል
እህል ያላመጠበትን የመጀመሪያ ቀን የሚያስታውስ የለም። ለነገሩ እህል ከማላመጣችን በፊት የፈረደባትን የ'ናታችንን ጡት ነክሰናል.. በሁለት የፊት ጥርስ እና ድድ የጡት ጫፍን ቅርጭው ይዘን.. ሁሉም እናቶች እሰይ ልጄ ጥርስ አበቀለች ብለው እንዳልተደሰቱ በምስራቻቸው ተነክሰዋል... ያውም እስከሚደሙ
****************************************
ይህ የራሴ ያገለገለኝ ንብረቴ ፡ ለሆነ አመት አፌ ሲከፈት ነጫጭ ሆኖ ተደርድሮ፡ ግጥም ብሎ አፌን ሞልቶ የልጅነት ቆንጆ ሳቅ አልፈጠረልኝም?
ቆሎ ... ከቆሎም ሳይንገረገብ በደረቁ ጣ ጣ ጣ እያለ የተቆላ ሽንብራ አልከካሁበትም? መለልታ ከአንጓ ሳለይ ሸንኮራ አልመጠጥኩበትም? ይባስ ብዬ ተደብቄ እየሰረኩ ስኳር ቅሜ እየቆረጫጨምኩበት ይህ ጥርሴ እስኪቦረቦር ድረስ አንጀቴን በወለላ ጣዕም አላራስኩበትም?
ይህ የልጅነት ጥርሴ ለምን ከእኔ ኖሮ ፡ ከእኔ እንዳልተፈጠረ በአመታት ውስጥ ነቅነቅ አለ? ለምን መነቃነቁ አሰጋኝ? ለምን ... ለምን ያ ቆሎም ቆንጥሮ ያቀበለ፡ ሸንኮራም ሸንሽኖ ያጎረሰ የገንዛ እጄ፡ የእጄ ጣቶች ከድዴ የተሰካን ጥርስ አነቃንቆ ለመንቀል ታገለ?
እኔ በ እኔ አልተጣላንም? ያውም በልጅነቴ?
ብተወዉ በስብሶ በሽታ፡ ብነቅለው - ክብር አሳጥቼ - ከቤቴም ደጃፍ አፈር ምሼ ሳልቀብረው፡ ደብቄ በትንሽ ብልቃጥ ሳላስቀምጠው... ይባስ ብዬ ወደ ጣርያ፡ ያውም አሻግሬ ለወፍ እና ለአይጥ ዘምሬ 'ያንቺን ለኔ የኔን ላንቺ' እያልኩ መወርወሬ.. ተሻግሮ ወይ በእኛ ቤት፡ ወይ በእነ አሹ ቤት ጣሪያ ቋ ብሎ መውደቁን፡ መጣሉን ሲያረጋግጥልኝ፡ አልያም አጥር ዘሎ በጎረቤት ተክል ወድቆ ፀ...ጥ።
በመዳፌ አስቀምጬ ቢያሻኝ በሰው መሀል ጮክ ብዬ፡ ወይ በኔና በጥርሴ መሀል በሽኩሹክታ 'አመሰግናለሁ' ብዬ አልተሰነባበትንም! ... ው ር ው ር !
እንደ ቀላል የራስን ባለውለታ ጠላት አርጎ ማየት ፡ ከዳተኝነትን፡ ልጅነቴ አውቃለች።
*******************************************
እንዳላገለገለን፡ እንዳላኗኗረን፡ የማይጠረቃው ሆዳችንን ጥያቄ እየከካ የሚመልሰው፡... የጡረታ ጊዜው ሲደርስ ክብር ያጣው
ነገሩ ሁሉ እንደ ጥርስ ይመስላል

አስተያየቶች

  1. ብዙዎቻችን ትንቢቶችን ተረት ፣ የደብተራ ቅዠት ወዘተ ብለን ስናናቅ ነበር የከረምነው። ትንቢት አትናቁ። የአበውን ቃል አትናቁ። የኢትዮጵያ መፍትሔ ፦ የእግዚአብሔር መንገድ ነው። በእግዚአብሔር መንገድ ውስጥ እውነተኛ ሰላም ፣ ፍትህ ፣ ጥበብ እና ተስፋ አለ።
    አንዳንዴ በምናየው ልክ ነው የምናስበው። ያላየነው የህይወት ገፅታ ስላላየነው አይሆንም የለም ማለት አይደለም። አንዳንዶች አሻግረው ተመልክተው የተለያዩ ገፅታዎችን ይመለከታሉ። ይህ የብስለት ጉዳይ ነው። የመንፈስ ብስለት አንድም ደግሞ የነፍስ ንቃት እና ትጋት ውጤት ነው።
    ኢትዮጵያ ትንሳኤ አላት የላትም ንትርክ ውስጥ መግባት አያስፈልግም። ትንሳኤውን አሻግረው ለተመለከቱ ትንሳኤው በፈቃደ እግዚአብሔር ጊዜውን ጠብቆ ይገለጥላቸዋል።
    ኢትዮጵያ ትንሳኤ እንዳላት ማመን እጅና እግርህን አጥፈህ ተቀምጠህ ጠብቅ ማለትም አይደለም።
    ሁሉም ነገር የትጋት ውጤት ነው። ነጥቡ እንዴት ነው የምንተጋው ነው። ቅኝ ገዥዎችህ ባስተማሩህና በሰሩልህ የፓለቲካ ርእዮተ ዓለም ነው በጥንቱ የአባቶችህ በነዮቶር ስርአት ነው ለኢትዮጵያ የምትተጋው ???
    በኢትዮጵያ ትንሳኤ የምናምነው ስራ ፈት ስለሆንን አይደለም። በቅዱሳት መፃሕፍት ፣ በቅዱሳን አባቶች ትንቢት እና በትውፊት ስለምናምን ነው። የኢትዮጵያን ትንሳኤ መጠበቅህ በእምነትህ ያጠነክርሃል እንጂ አያዝልህም።
    የዚህ ትንሳኤ መገለጥ ዝቅ የሚያደርጋቸው ስማዝያውያን (ሃያላን መንግሥታት) የኢትዮጵያ ትንሳኤ ሳይገለጥ ለማዳፈን እጅግ የረቀቁ ሴራዎችን አድብተው ሰርተዋል እየሰሩ ነው።
    ይህ ስልት አገር ውስጥ ባሉ የእናት ጡት ነካሾም የሚደገፍ ነው። አንዳንዶቹ ደግሞ በኢትዮጵያ ትንሳኤ ስም እየማሉ ከተዋህዶ ህዝቡን ሊለዩ የሚዳክሩትም የዛኑ ያህል ብዙ ናቸው።
    ትንሳኤውን ለማየት የቀራንዮን የስቃይና የፈተና መንገድ ማለፍ የግድ ነው! የሕዝባችን ወቅታዊ ሁኔታም ይህ ነው! ከመንገድ መሀል ነን! ጉዞ ላይ ነን! ከግቡ አልደረስንም! የትንሳኤውን ብርሀን እንድናይ የፈተናውን መንገድ ማጠናቀቅ አለብን! ጌታችን መድሀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በህይወታችን ውስጥ ያሉትን ፈተናዎችና መሰናክሎች የምናልፍበትን ጥበብ ትዕግስት ማስተዋል እና ፅናት እንዲሰጠን እመኛለሁ! የትንሳኤውን ብርሀን ለማየት ያብቃን!
    ውድ ኢትዮጵያውያን ሀገራችን ካለችበት ወቅታዊ ችግር በቅርብ እንድትላቀቅ ሁላችንም ሀላፊነት ስላለብን የምናስተላልፋቸው መልዕክቶችና መረጃዎች ሀላፊነት የሚሰማን እንደሆንን የሚመሰክሩ ሊሆኑ ይገባል ፈጣሪ ደግ ዘመን ያምጣልን !

    ምላሽ ይስጡሰርዝ

አስተያየት ይለጥፉ

ከዚህ ጦማር ታዋቂ ልጥፎች

አይሰው

እቴጌ ጣይቱ ብጡል (ብርሀን ዘ ኢትዮጵያ)

ደራሲ ዶ/ር ሀዲስ ዓለማየሁ (ሃዲስ ኣለማየሁ)